ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ የ2008 ዓ.ም ዐቢይ ጾምን አስመልክተው መልእክት አስተላለፉ
ቃለ በረከት ዘብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ዘተናገረ በእንተ በዓተ ጾም ዓቢይ ዘእግዚእነ ወአምላክነ ወመድኃኒነ ኢየሱስ ክርስቶስ ሎቱ ስብሐት፡፡
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን
በሀገር ውስጥና ከሀገር ውጭ በተለያዩ ክፍላተ ዓለም የምትገኙ የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ሕዝበ ክርስቲያን በሙሉ፤
ምሕረቱ የበዛ መዓቱ የራቀ ቸርና ሰው ወዳጅ የሆነው እግዚአብሔር አምላካችን እንኳን ለሁለት ሺሕ ስምንት ዓመተ ምሕረት የጌታችን፣ የአምላካችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ መዋዕለ ጾም ዓቢይ በሰላም አደረሳችሁ !!
‹‹ወአንሰ መጻእኩ ከመ ይርከቡ ሕይወተ ወፈድፋደ ይርከቡ፣ እኔ የተትረፈረፈ ሕይወት እንዲያገኙ መጣሁ›› (ዮሐ10፡10)
ይህ ቃል የሕይወት አስገኚና ሰጪ የሆነው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሰው ልጆች ዘላቂና ዘላለማዊ ሕይወት ሊሰጥ ሰው ሆኖ ወደሰዎች እንደመጣ ሲያመለክት የተናገረው ቃለ አድኅኖ ነው ፡፡
ለፍጡራን ሁሉ ትልቁና የመጀመሪያው ጸጋ ሕይወት ነው፤ ሰውም ሆነ ሌሎች ፍጥረታት በዚህ ዓለም ሲወጡና ሲወርዱ የሚገኙት ሕይወትን ለመንከባከብ፣ ለመጠበቅና ለማስቀጠል ነው፤
ምክንያቱም ሕይወት ካለ በሕይወት መሣሪያነት ሁሉም ይገኛል፤ ሕይወት ከሌለ ግን ሁሉም የለምና ነው ፡፡
በመሆኑም ሕይወት በፍጡራን ዘንድ ተወዳዳሪና መተኪያ የሌላት ሀብት ናትና ሙሉ ጥበቃና እንክብካቤ ሊደረግላት ይገባል ፤
አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋችንንና ነፍሳችንን በመዋሐድ ፍጹም አምላክ፣ ፍጹም ሰው ሆኖ በዓለም ላይ የተገለጠው ሕይወታችንን ለመጠበቅ፣ ለመንከባከብና ለማዳን ነው ፡፡
መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምድር ላይ ተገልጦ ይመላለስ በነበረበት ጊዜ ሕይወትን አጥተው በጉስቁልና የነበሩ የተለያዩ ሕሙማን ሕይወተ ሥጋን እንዲያገኙ አድርጎአል፤
ሕይወተ ነፍስን አጥተው የነበሩትም በሕያው ትምህርቱ ተስፋ ሕይወትን እንዲላበሱ አድርጎአል፤ ከዚህም በተጨማሪ በርካታ ሙታን ሕይወታቸውን ተጎናጽፈው ከመቃብር እንዲነሡ አድርጎአል፤ በእነዚህ ሁሉ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሕይወት ራስ መሆኑን ከመግለጽ ጋር ለሰው ልጆች ሁሉ ሕይወትን ለመስጠት እንደመጣ በትምህርትም በተግባርም አሳይቶአል ፡፡
ከዚህ አንጻር ሕይወት በፈጣሪም ሆነ በፍጡራን ምን ያህል ታላቅ ዋጋ እንዳላት
ማስተዋሉ አይከብድም፡፡
የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት፤
የሕይወት አስፈላጊነት ብዙ የሚያነጋግር አይሆንም ነገር ግን ሕይወትን በመጠበቅና በመንከባከብ ዙሪያ ብዙ ነገሮችን ማየቱ ተገቢ ነው ፤
ከሁሉ በፊት ማየት ያለብን የሰው ሕይወት ተፈጥሮ ነው፤ የሰው ሕይወት አስኳል የሆነች ነፍስ በሥራዋ ምክንያት ተቀጪ ወይም ተሸላሚ ትሆናለች እንጂ ህልውናዋ አይጠፋም፤
ህላዌ ነፍስ በዚህ ዓለምም ሆነ በላይኛው ዓለም የማያልፍና ቀጣይ ነው፤ ነገር ግን በቅጣት የምትኖሮው ህላዌ ነፍስ እንዳለመኖር ስለሚቆጠር በመንፈሳዊ ርእይ እንደሞተች ወይም እንደጠፋች ይቆጠራል፤
በመሆኑም ይህ ዓይነቱ መጥፎ ቅጣት በሰው ሕይወተ- ነፍስ እንዳይደርስ ነው ጌታችን ሕይወትን እንዲያገኙ መጣሁ ያለው፤
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሕይወተ – ነፍስ ሲባል እርሱ የሕይወትን ዋጋ ከፍሎ የሰው ሕይወተ ነፍስን በመሥዋዕትነቱ ከቅጣት የምትድንበትን ዕድል አመቻቸቶአል ነገር ግን በዚህ ጠባብ በር ገብቶ ለመዳን አሁንም በሰዎች በኩል ተጋድሎው መቀጠል የግድ ይላል፡፡
የተጋድሎ ጉዞ መነሻው እምነት ነው፤ መጓጓዣውም ሥነ ምግባር ነው፤ መዳረሻው ደግሞ ከቅጣት ነጻ የሆነች የዘላለም ይሕወትን መቀዳጀት ነው፡፡
በዓርባ ወይም በሰማንያ ቀን ሀብተ ክርስትና፣ ስመ ወልድ ያገኙ አማንያን ክርስቲያኖች የጉዞው መነሻ አጠናቀዋል አሁን የሚገኙት በመካከለኛው መንገድ ሆኖ ሃይማኖትን በሥነ ምግባር በሚገልፁበት ጎዳና ላይ ናቸው፤ ይህ ጎዳና ጠበብ ያለ ስለሆነ ጥበብና ጥንቃቄ ያስፈልገዋል ፡፡
በዚህ ጉዞ ፈቃደ ሥጋ በእጅጉ ይዋጋል፤ እርሱ ካሸነፈ ሕይወት ለቅጣት ትዳረጋለች፤ ፈቃደ ነፍስ ካሸነፈ ደግሞ ሕይወት ከቅጣት ነጻ ትሆናለች ፡፡
ነገሩ እንደዚህ ከሆነ ፈቃደ ሥጋ እንዲሸነፍ፣ ፈቃደ ነፍስ እንዲያሸንፍ በዋናነት መሣሪያ ሆኖ የሚያገለግል ጾም ነው ፡፡
የጾም መሠረታዊ ዓላማ የሥጋ ፍላጎት የሆነውን ሁሉ በመግታት ብሎም በማስወገድ ለነፍስ ፍላጎት ማደር፣ መታዘዝና መገዛት ነው፤ ይህም ማለት ለእግዚአብሔር መታዘዝ፣ መገዛትና አምልኮ ማቅረብን ያጠቃልላል፤
በሌላ አባባል ፈቃደ ነፍስን መፈጸም ማለት ፈቃደ እግዚአብሔርን መፈጸም ማለት ነው፤ ምክንያቱም ሰው በእግዚአብሔር አርአያና አምሳል የተፈጠረ ነው ሲባል የሰው ፈቃደ ነፍስ በባህርዩ ወደ ፈቃደ እግዚአብሔር የያደላ ነው ማለት ነው ፡፡
በመሆኑም ሰው ምንጊዜም ቢሆን ፈቃደ ሥጋውን እየገታ፣ ፈቃደ ነፍሱን እያስተናገደ መኖር እንደሚገባው ቢታወቅም በተለይም እኛን ክሶ ለማዳን ሲል ጌታችን የጾመውን ጾም መነሻ በማድረግ ይህን ጾመ ኢየሱስ በተለየ ሁኔታ እንጾመዋለን፤
በዚህም ፈቃደ ሥጋን በቁጥጥር ሥር አውለን ፈቃደ ነፍስን ዋና መሪና አለቃ በማድረግ በሁሉም ነገር እግዚአብሔርን እናመልካለን እናመሰግናለን ለእርሱም ብቻ እንታዘዛለን እንገዛለን በዚህም መንፈሳዊ መሣሪያ ነፍሳችንን ከቅጣት እንጠብቃለን ፡፡
የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናን ወምእመናት፤
ፈቃደ ሥጋንና ፈቃደ ነፍስን ለይቶ ለማወቅ ብዙ ውጣ ውረድ አያስፈልግም፤ ምክንያቱም ኅሊናችን ለይቶ ያውቃቸዋልና ነው፤ ይህም ማለት ኅሊናችን የማይስማማበት ሁሉ ፈቃደ ሥጋ ነውና እርሱን መተው አለብን ማለት ነው፤ ኅሊናችን የሚስማማበት ግን ፈቃደ ነፍስ ነውና እርሱን ማድረግ አለብን
እውነቱን መለየት በሚያቅተን ጊዜ ደግሞ መጻሕፍትን በማንበብና መምህራንን በመጠየቅ መረዳት እንችላለን ፡፡
ዋናውና ታላቁ ኃጢአት ኅሊናችን ያልተስማማ ሆኖ እያለ እርሱን በፈቃደ ሥጋ ተገፍተንና ተሸንፈን የምንፈጽመው በደል ነው፤
ይህ ዓይነቱ ባሕርይም በውስጣችን አለና እርሱን በጽናትና በመንፈሳዊ ብርታት ተዋግተን ማሸነፍ አለብን፣ ማለትም ለዚህ መንበርከክና መሸነፍ የለብንም ማለት ነው፡፡
ብዙ ክርስቲያኖች ጾምን በተመለከተ ቶሎ ትዝ የሚላቸው የእንስሳት ተዋጽኦ የሆነውን አለመመገብ፣ እስከ ተወሰነ ሰዓት ቆይቶ መመገብ ብቻ ነው፡፤
ይሁን እንጂ ይህ እንዳለ ሆኖ ሌሎች ዓበይት የጾም ሠራዊትም እንዳሉ ማስተዋሉ ተገቢ ነው ፡፡
ጾም ማለት ፊደላዊ ትርጉሙ መተው ማለት ነውና ምግብ ብቻ ሳይሆን ብዙ የምንተወው አለ፣ የምናደርገውም አለ፡፡
መተው ካለባቸው ነገሮች መካከል ተድላ ሥጋን፣ መጣላትን፣ መጨካከንን፣ ፍትሕ ማጉደልን፣ ሰው መበደልን፣ ምቀኝነትን፣ መናናቅን፣ መነታረክን፣ መጨቃጨቅን፣ ራስ ወዳድነትን፣ አልጠግብ ባይነትን፣ ለብቻ መብላትን፣ ሥራ ፈትነትን መካሰስን፣ የሌላው መሻትን፣ የመሳሰሉ ሁሉ መጾም አለባቸው ማለትም መተው አለባቸው ፡፡
በሌላ በኩል በጾም ወቅት መደረግ ያለባቸው መራራትን፣ መጸለይን፣ አብዝቶ መዋደድን፣ ተደጋግፎና ተባብሮ መኖርን፣ የተራበውን ማብላት፣ የተጠማውን ማጠጣት፣ የታረዘውን ማልበስ፣ ያዘነውን ማጽናናት፣ የታመመውን መጠየቅ፣ የታሠረውን መጎብኘት፣ እንግዳን ተቀብሎ ማስተናገድ፣ በሁሉም ነገር የሰላም ጠበቃ ሆኖ መገኘት፣ ፍትሕን መስጠት ለድሀና ለችግረኛ ቅድሚያ በመስጠት ማገዝ፣ የተገፋውን መርዳት ሁልጊዜ የእግዚአብሔርን ፈቃድ መጠየቅና ያንኑ ማድረግ ወዘተ የመሳሰሉ መተግበርና በሥራ ማዋል ይገባል ፡፡
በመሆኑም ሕዝበ ክርስቲያኑ በዚህ መዋዕለ ጾም መንፈሳዊ ተግባራትን ከመፈጸም ጎን ለጎን እያንዳንዱ ዜጋ ለሀገሩ ልማት ጥቅምና ብልፅግና በአርቆ አስተዋይነት እንዲቆም፣ የሀገራችንና የሕዝቦቻችንን አንድነትና ወንድማማችነት ከሚፈታተን መጥፎ ድርጊት ሁሉ በመቆጠብ ወደልማትና ወደ ዕድገት ብቻ እንዲሠማራ፣ ጾሙም ጸሎቱም በእግዚአብሔር ፊት ተቀባይነት ኖሮት ለሀገራችንና ለሕዝቦቻችን የሕይወት ስኬት ሊያመጣልን የሚችለው በፍቅርና በስምምነት አንድ ላይ ስንጾም ስለሆነ፣ መላው የሀገራችን ሕዝቦች በያላችሁበት ሰላማችሁን፣ ወንድማማችነታችሁንና አንድነታችሁን በመጠበቅ፣ በድርቁ ምክንያት የተጎዱ ወገኖቻችንን በመርዳት የጾሙን ወራት እንድታሳልፉ በእግዚአብሔር ስም መልእክታችንን እናስተላልፋለን ፡፡
እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
አሜን
አባ ማትያስ ቀዳማዊ
ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ
ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት
የካቲት 28 ቀን 2008 ዓ.ም
አዲስ አበባ
ኢትዮጵያ
{flike}{plusone}