የአዲስ አበባና ጉራጌ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብጹዕ አቡነ መልከ ጼዴቅ የሕማማትና የትንሣኤ በዓላትን አስመልክቶ መመሪያ አስተላለፉ!!

ሚያዚያ 14 ቀን 2013 ዓ.ም የአዲስ አበባና ጉራጌ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስን ጨምሮ የሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ መ/ር አካለወልድ ተሰማና ልዩ ልዩ የሥራ ኃላፊዎች በተገኙበት በሀገረ ስብከቱ የስብሰባ አዳራሽ የሰሙነ ሕማማትና የትንሣኤ በዓላት አከባበር መንፈሳዊ ይዘቱን ጠብቆ እንዲከበር አባታዊ መመሪያ አስተላልፈዋል፡፡
ከሆሳእና ጀምሮ ያሉት የሕማማትና የትንሣኤ በዓላት ልዩ ልዩና በርካታ መንፈሳዊ ሥርዓቶች የሚፈጸሙባቸው በዓላት በመሆናቸው ከአገልጋይ ካህናት ጀምሮ ሁሉም የበዓሉ ተሳታፊ ምዕመናን ራሳቸውን በከፍተኛ ፍጥነት እየተስፋፋ ከሚገኘውና ብዙ ወገኖቻችንን ካሳጣን የCovid-19 በሽታ ራሳቸውን እንዲጠብቁና የወጣውን አዲስ መመሪያ እንዲያከብሩና ከጸጥታ አካላት ጋር ተናበው የአካባቢያቸውን ሰላም ጠብቀው እንዲያስጠብቁ አሳስበዋል፡፡
አያይዘውም ከበዓላት መከበር ጋር ተያይዞ የሚዲያ አካላት በዓሉን አስመልክተው የሚጋብዟቸው እንግዶች በትውውቅና በመጠቋቆም ሳይሆን የቤተ ክርስቲያንን ድምፅ በትክክል የሚያሰሙና ቤተ ክርስቲያንን የሚወክሉ እንዲሆኑ በሀገረ ስብከቱ ሕዝብ ግንኙነት በኩል ለሁሉም የሚዲያ አካላት ደብዳቤ መጻፉ አሳውቀው፡፡
ዘጋቢ፡- መ/ር ሽፈራው እንደሻው